ምድር ባቡርን ጨምሮ ስድስት የመንግስት ልማት ድርጅቶች 50 ቢሊዮን ብር እዳ እንዳለባቸው ተገለጸ። የመስኖ እና ቆላማ አካባቢዎች ሚንስቴር 1 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር ለማን መክፈል እንዳለበት አይታወቅም ተባለ።

የፌደራል ዋና ኦዲተር የ2015 በጀት ዓመት የፌደራል መንግሥት ተቋማትን የበጀት ኦዲት ሪፖርትን ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አቅርቧል።

ተቋሙ በዚህ ሪፖርቱ ላይ እንዳለው 14 የመንግስት ተቋማት 1 ነጥብ 7 ቢሊዮን ብር በተከፋይ በጀት የያዙ ቢሆንም ለማን መከፈል እንዳለበት እንደማይታወቅ አስታውቃል።

ከነዚህ ተቋማት መካከል የመስኖ እና ቆላማ አካባቢ ሚንስቴር 1 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር፣ የኢኖሼሽን እና ቴክኖሎጂ ሚንስቴር 132 ሚሊዮን ብር እንዲሁም ማዕድን ሚንስቴር ደግሞ 30 ሚሊዮን ብር ለማን እንደሚከፍሉ አያውቁም ተብላል።

ተቋማቱ ብሩን በወቅቱ መከፈል ላለበት ባለ መብት በቶሎ አለመክፈላቸው የመንግሥትን እዳ እያናሩ በመመሆኑ እንዲስተካከል ጠይቋል።

ሌላኛው የፌደራል ዋና ኦዲተር በሪፖርቱ የጠቀሰው ጉዳይ በፌደራል መንግሥት የሚገነቡ ፕሮጀክቶች ጉዳይ ሲሆን ህግ ተጥሶ ስራ ተቋራጮች ፕሮጀክቶችን ያላግባብ እንዲይዙ መደረጉ ነው።

የስራ ተቋራጮች ከዚህ በፊት የነበራቸው የስራ አፈጻጸም ሳይታይ በሌሎች የግንባታ ጨረታዎች ላይ እንዲወዳደሩ እና እንዲገነቡ መደረጉን ዋና ኦዲተሩ አስታውቋል።

11 ቢሊዮን ብር ገደማ ዋጋ ያላቸው 12 የግንባታ ፕሮጀክቶች ለሁለት የስራ ተቋራጮች መያዛቸው የህግ ጥሰት መፈጸሙ በሪፖርቱ ላይ ተገልጿል።

የግንባታ ፕሮጀክቶች መቋረጥ መንግስትን ለሀብት ብክነት እየዳረገው ነው ያለው የፌደራል ዋና ኦዲተር ሪፖርት ለናሙና ከታዩ 41 የተቋረጡ ፕሮጀክቶች መንግስትን ለ17 ቢሊዮን ብር ተጨማሪ ወጪ እንዲያወጣ እድርገዋል ተብሏል።

ግንባታዎችን የሚቆጣጠረው የኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን ባለስልጣን ግንባታዎች ከተቋረጡ በኋላ የተከፈሉ የቅድመ ክፍያዎችን አለማስመለስ እና የመልካም ስራ አፈጻጸም ዋስትና ገንዘብን ተከታትሎ እንዳላስፈጸመም በሪፖርቱ ላይ ተገልጿል።

እንዲሁም በኢትዮጵያ ህንጻ፣ መንገድ እና ልዩ ልዩ ስራ ተቋራጭነት ዘርፍ ፈቃድ ከወሰዱ 261 የውጭ ሀገራት ስራ ተቋራጮች ውስጥ ስራ ላይ ያሉት 11 ብቻ ሆነው እያለ ቀሪዎቹ በምን ሁኔታ ላይ እንዳሉ ቁጥጥር እና ክትትል እንዳልተደረገባቸውም የኦዲት ሪፖርቱ ያስረዳል።

የምድር ባቡር ኮርፖሬሽንን ጨምሮ በመንግስት የልማት ድርጅቶች ይዞታ እና አስተዳድር ስር የሆኑ ስድስት ተቋማት እስከ መስከረም 2016 ድረስ ያለባቸው እዳ 50 ነጥብ 8 ቢሊዮን ብር ደርሷል ተብሏል።

እንዲሁም እነዚህ ተቋማት ከ2013 እስከ 2015 ዓ .ም ሳይሰበሰብ የቀረ 12 ቢሊዮን ብር ውዝፍ የትርፍ ድርሻ እዳ እንዳለባቸውም ተገልጿል።

By Al Ain Amharic News

አል ዐይን ኒውስ ሁሉን አቀፍ ሽፋን የሚሰጥ እና የዓለም ክስተቶችን በወቅቱና በጊዜው ለተከታዮቹ ያቀርባል፡፡

One thought on “የመስኖ እና ቆላማ አካባቢዎች ሚንስቴር 1 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር ለማን መክፈል እንዳለበት አያውቅም ተባለ”

ምላሽ ይስጡ

ኢ-ፖስታ አድራሻወ ይፋ አይደረግም። መሞላት ያለባቸው መስኮች * ምልክት አላቸው