ሰኞ ሰኔ 10 ቀን 2016 (አዲስ ማለዳ) የአዲስ አበባ ከተማ አሥተዳደር የትምህርትና ስልጠና ጥራት ቁጥጥር ባለስልጣን የ41 ትምህርት ቤቶች ፈቃድ መሠረዙን አስታወቀ፡፡

ፈቃዳቸው የተሠረዘው ትምህርት ቤቶች የትምህርት ፖሊሲውን ባለመጠበቅና መስፈርቱን ባለማሟላታቸው ነው ብሏል ባለስልጣኑ፡፡

ባለስልጣኑ በ2017 ዓ.ም የትምህርት ዘመን ተማሪዎችን መዝግበው የሚያስተምሩ ትምህርት ቤቶችን እና ፈቃዳቸው የተሠረዘ የትምህርት ተቋማትን ይፋ አድርጓል፡፡

ከእነዚህ ትምህርት ቤቶች መካከልም የካ፣ ልደታ ጉለሌና ንፋስ ስልክ ክፍለ ከተማ የሚገኙ የጊብሰን ትምህርት ቤቶች፣ የቅዱስ ሚካኤል አምስት ትምህርት ቤቶች፣ የካ አፖሎ ትምህርት ቤት ይገኙበታል ተብሏል።
በዚህም በ2017 ዓ.ም የትምህርት ዘመን ተማሪዎችን መዝግበው የሚያስተምሩ ትምህርት ቤቶች 1 ሺህ 332 ሲሆኑ÷ የማስተማር ፈቃድ እንደተሰጣቸውም ገልጿል፡፡

በሌላ በኩል 43 ትምህርት ቤቶች በራሳቸው ጊዜ መቀጠል ስላልቻሉ ፈቃዳቸው ተሠርዟል መባሉን የባለስልጣኑ መረጃ አመላክቷል፡፡

እንዲሁም 150 ትምህርት ቤቶች ጉዳያቸው በሂደት ላይ መሆኑና ወደፊት እንደሚገለጽ ተጠቁሟል፡፡
41 ትምህርት ቤቶች ደግሞ የትምህርት ፖሊሲውን ባለመጠበቅና መስፈርቱን ባለማሟላታቸው ፈቃዳቸው መሠረዙን አዲስ ማለዳ ከመግለጫው ሰምታለች፡፡
ዕገዳ በተጣለባቸዉ ትምህር ቤቶች ይማሩ የነበሩ ተማሪዎች በመኖረያ አቅሪያቢያቸዉ በሚገኙ የግልና የመንግስት ትምህርት ቤቶች ያለምንም ተጨማሪ ክፍያ እንዲስተናግዱ ይደረጋል ተብሏል።

By Addis Maleda

አዲስ ማለዳ ወቅታዊ የአገራችንን ጉዳዮች በስፋትና በጥልቀት የምትተነትን፣ የብዙኃን መገናኛ ናት።

ምላሽ ይስጡ

ኢ-ፖስታ አድራሻወ ይፋ አይደረግም። መሞላት ያለባቸው መስኮች * ምልክት አላቸው